ቅዱስንን በካህናት ልብ እና ክብር ተነስተው ማየት
ለወደደንና ከኅጢአታችንም በደሙ ነጻ ላወጣን፣ አምላኩንና አባቱን እንድናገለግልም መንግሥትና ካህናት ላደረገን፣ ለእርሱ ክብርና ኅይል ከዘላለም እስከ ዘላለም ይሁን አሜን።
ራዕይ 1፡6
የካህናት አገልግሎት አስተባባሪ
ቅዱስንን በካህናት ልብ እና ክብር ተነስተው ማየት
ቅዱሳንን በሰማያዊ ሕዝብ ማንነት መገንባት እና ቅዱሳን ካህናት እንዲሆኑ መስራት
የሰማያዊ መንግስት ሕይወት እና ክብር መግለጥ
ካህን የሚለው ቃል የዕብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጓሜውም አገልጋይ ማለት ነው። ካህን በተቀደሰው ነገር ላይ እንዲያገለግል፤ በመሰውያ ላይ መስዋዕትን እንዲያቀርብ፤ በእግዚአብሔር የተሾመ እና በእግዚአብሔር እና በሰው መካከል መካከለኛ እንዲሆን፥ በእግዚአብሔር የተመረጠ አገልጋይ ነው። ካህናት ለሕዝቡ የእግዚአብሔር እውቀት ምንጭ እና መንፈሳዊ ሕይወት የሚፈስባቸው የከበሩ ደጆች ናቸው። የክህነት ታሪክ ከጥፋት ውሃ በኋላ፥ የሰው ዘር ሁሉ አባት በሆነው በኖህ የሚጀምር ሲሆን የእስራኤል ሕዝብ አባቶች በሆኑት፤ በአብርሃም፣ በይስሐቅ እና በያዕቆብ ዘመንም፤ ከእግዚአብሔር ጋር ሕብረት ለማድረግ፤ የክህነት ስርዓት ይፈጸም ነበር። እግዚአብሔር የእስራኤልን ሕዝብ ከግብጽ ባርነት፥ በሙሴ በኩል ነጻ ካወጣቸው በኋላ፤ ለራሱ ከአህዛብ ሁሉ የተመረጠ ርስት፣ የካህናት መንግስት እና የተቀደሰም ህዝብ እንደሚያደርጋቸው ተስፋን ሲሰጣቸው እንመለከታለን (ዘጸ 19፥5 6)። የካህናት መንግስት ማለት የእስራኤል ህዝብ ሁሉ፥ የእስራኤል መንግስት አገልጋይ ሲሆን ማለት ነው። በተጨማሪም እስራኤል መንግስት ሆና ከተመሰረተች በኋላ፤ በተቀደሰ ክብር እና ስልጣን፤ የእስራኤልን ሕዝብ ያገለግሉ ዘንድ፤ በየቤተሰቡ የሚወለዱ በኩራት ወንዶች ልጆች ለክህነት ተመረጡ፤ ነገር ግን በመጨረሻ የኩሮች ምትክ ሆነው፤ የሌዊ ነገድ እና የአሮን ቤተሰብ የክህነትን ክብር ተቀበሉ።
በብሉይ ኪዳን የሌዊ ነገድ የሆኑትን ካህናት በሶስት የስልጣን እርከን እና ኃላፊነቶች ልንከፍላቸው እንችላለን፤ እነርሱም
1ኛ/ አሮን (ሊቀ ካህናት)
2ኛ/ የአሮን ቤተሰብ (ካህናት)
3ኛ/ ሌዋውያን (የካህናት ረዳቶች ወይም አገልጋዮች) ናቸው።
ክህነት በውስጡ በልዩ ልዩ የአገልግሎት አይነቶች እና ኃላፊነቶች የተከፋፈለ ቢሆንም ነገር ግን ሁሉም አንድ እና ብቸኛ አምላካቸውን፣ አንዱን የእግዚአብሄር ማደሪያ የሆነውን የመገናኛ ድንኳን፣ አንዱን የእስራኤል ሕዝብ እና መንግስት፣ አንዱን የእግዚአብሄር ሕግ እና ስርዓት እንዲሁም ለአንድ ተስፋ እና ፍጻሜ እንደ አካል ያገለግሉ ነበር።ብሉይ ኪዳን የአዲስ ኪዳን ጥላ ሲሆን አዲስ ኪዳን ደግሞ በአንጻሩ የብሉይ ኪዳን መንፈሳዊ አካል ነው። ክህነት በአዲስ ኪዳን፤ አሮጌ እና ከንቱ ከሆነ አካላዊ ስርዓት እውነተኛ ወደ ሆነው መንፈሳዊ ስርዓት፣ ከስጋዊ መስዋዕት እግዚአብሔርን ደስ ወደሚያሰኝ መንፈሳዊ መስዋዕት፣ ከሌዊ ነገድ ወደ ይሁዳ ነገድ፣ ከአሮን ሊቀ ክህነት በመልከ ጼዴቅ ሹመት ካህን ወደ ሆነው ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ከእስራኤል ሕዝብ እና መንግስት ወደ እግዚአብሔር ሕዝብ እና መንግስት (ቤተክርስቲያን)፣ ከሕግ አገልግሎት ወደ መንፈስ ቅዱስ አገልግሎት ተሸጋግሯል።
በአዲስ ኪዳን ካህናት የእግዚአብሔር የጥበብ እና የእውቀት መዝገብ የሆነውን ክርስቶስን የሚገልጡ እና የሚያገለግሉ ናቸው። በተለያዩ የአገልግሎት ስጦታዎች እና ኃላፊነቶች የሚያገለግሉ ቢሆንም፤ አንዱን አባት እና አምላክ፣ አንዱን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን፣ በአንዱ በመንፈስ ቅዱስ፣ አንዱን የእግዚአብሔርን መንግስት፣ ለአንድ ተስፋ እና ፍጻሜ እንደ አካል የሚያገለግሉ ናቸው። ቅደሳንን ሁሉ በሰማያዊ ሕዝብ ማንነት የመገንባት እና እንደ ተቀደሱ ካህናት የመስራት ሸክም እና ኃላፊነት አለባቸው። “አምላኩንና አባቱን እንድናገለግልም መንግሥትና ካህናት ላደረገን፣ . . .” ( ራእይ 1፥6) ተብሎ እንደተጻፈ እያንዳንዱ አማኝ ዳግም ሲወለድ ክህነትን ከክርስቶስ ተካፍሏል፤ ስለዚህ ሕይወታችንን ለሞተልን እና ስለ እኛ ከሞት ለተነሳልን እንጂ ከእንዲህ ወዲህ ለራሳችን እንዳንኖር አንዱ ስለ ሁሉ ሞተ።
“እናንተ ደግሞ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ አማካይነት እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕት ታቀርቡ ዘንድ፣ ቅዱሳን ካህናት ለመሆን እንደ ሕያዋን ድንጋዮች መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ትሠራላችሁ።” — 1ኛ ጴጥሮስ 2፥5 (አዲሱ መ.ት) በማለት ራሳችንን ቅዱስ መስዋዕት አድርገን እንድናቀርብ እና በክርስቶስ የተካፈልነውን የክህነት ስልጣን እና ክብር ወደ ሙላት እንድናመጣው ያስተምረናል
"¯ስጦታዎች ልዩ ልዩ ሲሆኑ፣ መንፈስ ግን አንድ ነው፤ አገልግሎትም ልዩ ልዩ ሲሆን፣ ጌታ ግን አንድ ነው፤ አሠራርም ልዩ ልዩ ሲሆን፣ ሁሉን በሁሉ የሚሠራው ግን ያው አንዱ እግዚአብሔር ነው።"
1ኛ ቆሮንቶስ 12